Friday, 21 September 2012

ቅዱስ ያሬድ ዜማውና 1500ኛ አመት
መታሰቢያ ክፍል ሁለት
1500ኛ ዓመት የቅዱስ ያሬድን በዓል
ምክነያት በማድረግ በክፍል አንድ ስለ
ቅዱስ ያሬድ "ሊቁ ቅዱስ ያሬድ ዜማውና
1500ኛ አመት መታሰቢያ ክፍል አንድ"
በሚል ርእስ አስነብበናችኋል፡፡ ዛሬ ደግሞ
በክፍል ሁለት የቅዱስ ያሬድ የዜማ ስልት
በሚል ይዘንላችሁ ቀርበናል፡፡
ሀገራችን ኢትዮጵያን ለጥቁር
ሕዝቦች መኩሪያ እንድትሆን ያደረጋት
የልጆቿ ሀገር ወዳድነትና ጀግንነትን
የተመላው ባህሏ ብቻ ሳይሆን የሃይማኖት፣
የሥነ ዜማ ሀገር መሆኗም መጻሕፍተ
ታሪክን ባነበቡ ሊቃውንት አንደበት ብቻ
ሳይሆን በማዳመጥ ትውፊት /ርክክብ/
ለኅብረተሰቡ ኀቡእ ያልሆነ ነገር መሆኑ ነው፡፡
” ለኢትዮጵያ ሰዎችም ምግባቸውን
ሰጠሃቸው።” መዝ.74:14 ለኢትዮጵያ
ከተሰጡት ታላላቅ ሀብቶች መካከል አንድ
በልዩ ስጦታ ከሰማያት ከመላእክት በቀር
የትም የማይገኝ እና የተም የሌለ
የቅዱስ ያሬድ የዜማ ስልት ነው፡፡
የቅዱስ ያሬድ የዜማ ስልት ግዕዝ
ዕዝልና አራራይ በሚባሉ ሦስት የዜማ
መደቦች ይመደባሉ፡፡ የሦስቱ መደቦች
የዜማ ድምፃቸው አንድ ሲሆን አንድ
መሆናቸው የሥላሴን አንድነት
የሚያመለክት ነው ፡፡ የዜማ ስልቶች
ግዕዝ፡- ግዕዝ ማለት ገአዘ ነፃ
ወጣ ማለት ሲሆን በዜማነቱ
ሲተረጎም የመጀመሪያ አንደኛ
ስልት የቀና ማለት ይሆናል
የዜማው ፀባይ ደረቅ ያለና ብዙ
እርክርክታ የሌለው ለጉሮሮ
ጠንካራ ኃይለኛ በመሆኑ
ሊቃውንቱ ደረቅ ዜማ ይሉታል
ዕዝል፡- የግዕዝ ድርብና ታዛይ
ነው ምሳሌነቱ የወልድ ሲሆን
ትርጓሜው ፅኑ ማለት ነው፡፡
ጌታችንና መድኃኒታችን ኢየሱስ
ክርሰቶስ ጽንዑ የሆነ መከራን
ተቀብሎ እኛን የአዳም ልጆች
ማዳኑን ያስረዳናል፡፡ አንድም
የመለኮትና የትስብእት ተዋህዶ
ረቀቅ ስለሚል ቀስ በቀስ
ሊማሩት እንደሚገባ ያስገነዝባል፡፡
አራራይ፡- የሚያራራ፣ ጥዑም
ልብን የሚመስጥ ማለት ነው፡፡
የዜማው ስልት ልብን የሚያራራ
በመሆኑ ስያሜውን አግኝቷል፡፡
ሐዋርያትን ከበዓለ ጴንጤቆስጤ
በኋላ ያረጋጋ ያጽናና እና ጥበዓተ
ድፍረት ሰጥቶ ዓለምን
እንዲያጣፍጡ ስላደረገ አራራይ
ዜማ በመንፈስ ቅዱስ ይመሰላል፡፡
በቤተ ክርስቲያን የሚቀርበው
ምስጋና በሙሉ በሦስቱ የዜማ ዓይነቶች
ነው ፡፡ ማንኛውም ሰው በቤተ
ክርስቲያናችን መዝሙር የሚያቀርበው
የቅዱስ ያሬድን የዜማ ምልክቶችና
ዓይነቶች /ስልቶች/ ተከትሎ ነው ፡፡
ሦስቱ የዜማ ዓይነቶች እራሳቸውን
ችለው የሚዜሙ ቢሆኑም አንዱ የዜማ
ዓይነት በሌላው የዜማ ዓይነት ውስጥ
የሚገኝ መሆኑ መታወቅ አለበት ፡፡
ለምሳሌ ያህል ከግዕዝ ከሚባለው ዜማ
ዓይነት ዕዝልና የአራራይ ዜማ ይወጣሉ
፡፡ ይህም በአሐዱ አብ ዜማ ይታወቃል፡፡
ምሥጢሩ ከአብ እምቅድም ዓለም
ወልድ ለመወለዱ ከመንፈስ ቅዱስ
ለመስረፁ ምሳሌ ነው፡፡ ከዚህም ጋር
የንባቡና የድምጹ ቃና አንድ መሆን
የሥላሴን አንድነት ሲያስረዳ የዜማው
ሦስት ዓይነት መሆን የሦስትነታቸው
ምሳሌ ነው፡፡ ይህ ሲባል ግን አንዱ
ሌላውን ይተካል ማለት ሳይሆን አንዱ
የዜማ ዓይነት በሌላው የዜማ ዓይነት
ውስጥ በተወሰነ መጠን ተመሳስሎ
ይገኛል ለማለት ነው ፡፡ ለምሳሌ የቅዳሴ
ጸሎት በሦስቱ የዜማ ዓይነቶች
የተቀመረ ሆኖ እናገኘዋለን ፡፡
ቅዱስ ያሬድ በግዕዝ፣ በዕዝል በአራራይ
ዜማውን እያስማማ ፈጣሪውን
እግዚአብሔርን ያመሰገነው በ22
አርእስተ ዜማ እያቀናበረ ነው ይኸውም
በ22ቱ ስነ ፍጥረት ምሳሌ ነው፡፡
የስነፍጥረት ምሳሌ የሆኑት 22 አርእስተ
ዜማ የሚከተሉት ናቸው::
1.ዋዜማ
2. በሐምስት
3. እግዚአብሔር ነግሠ
4.ይትባረክ
5.ሠለስት
6.ሰላም
7. መዝሙር /መሐትው አቡን/
8.ዘአምላኪየ
9.ሚበዝኁ
10. አርባዕት
11. ብጹዕ ዘይሌቡ
12. መወድስ
13. ኩልክሙ
14. ዕዝል
15. ዘይእዜ
16. እሰመ ለዓለም
17. እሰመ ለዓለም
18.አርያም
19. ክብር ይእቲ
20. ስብሐተ ነግሕ
21.ዝማሬ
22. ዕጣነ ሞገር
ይቆየን…….ይቀጥላል ከአንድ ቀን ብኋላ
ቀጣዩን ክፍል እናቀርባለን
++++++የቅዱስ ያሬድ በረከት ረድኤት
አይለየን፡፡ አሜን::+++++++++++

""ለቤተ ክርስቲያናችን ዛሬም ነገም እርስቷን ላናስነካ ቃልእንገባለን:: ቤተክርስቲያኔ ሆይ ብረሳሽ ቀኜ ትርወሳኝባላስብሽ ምላሴ ከትናጋዬ ይጣበቅ!!""

Wednesday, 19 September 2012

ቅዳሴን በካሴት ማስቀደስ ይቻላል?

በዲ/ን ኅሩይ ባየ
እድሜ ለቴክኖሎጂ ይድረስና ድካምን የሚቀንሱ በርካታ
የሥልጣኔ ውጤቶች እየተከሰቱ ነው፡፡ ከእነዚህ ውስጥ አንዱ
መቅረጸ ድምጽ ሲሆን ያለፈን ለማስታወስ የለው ጠቀሜታ
የጎላ ነው፡፡ መዝሙሮች ቅዳሴዎች፣ ትምህርቶች እና
የአባቶች ምክር በካሴትና በሲዲ በምስልና በድምጽ
እየተዘጋጁ የሚሰጡት አገልግሎት እጅግ ከፍ ያለ ነው፡፡
ቤተ ክርስቲያን ከምትገለገልበት ሥርዐተ አምልኮ መካከል
ቅዳሴ አንዱ ሲሆን በካሴት ተቀርጾ በገበያ ላይ ይሸጣል፡፡
እኔም ቅዳሴን በካሴት ከቤት ውስጥ ሆኖ ማስቀደስ ይቻላል
ወይስ አይቻልም? የሚል ጥያቄ በውስጤ ይመላለሳል፡፡
እባካችሁ ቅዳሴን በካሴት በቤት ውስጥ ሆኖ ማስቀደስ
ይቻል ወይም አይቻል እንደሆነ መልስ ስጡኝ?”
የተከበሩ ጠያቂያችን በቅድሚያ ስላቀረቡልን ጥያቄ
ምስጋናችንን ስናቀርብ ከልብ ነው፡፡ ማንነትዎንና ያሉበትን
ቦታ ስላልገለጡልን ለምንመልሰው መልስ አቅጣጫ
ለመጠቆም አልረዳንም፡፡ ቢሆንም መሠረታዊ የሆነው
ጥያቄዎ ስለተገለጠ አስቸጋሪ ነገር አይኖረውም፡፡
በኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን በሰንበት
ትምህርት ቤቶች ማደራጃ መምሪያ ማኅበረ ቅዱሳን የስምዐ
ጽድቅ ጋዜጣ አዘጋጅ የሆኑትን ሊቀ ጠበብት ሐረገወይን
አገዘን እና በማኅበረ ቅዱሳን የመጻሕፍት ዝግጅት ክፍል
አርታኢ የሆኑትን መምህር ተስፋ ሚካኤል ታከለ ለቀረበው
ጥያቄ ምላሽ እንዲሰጡን ጋብዘናቸዋል፡፡
ሊቀ ጠብብት ሐረገወይን “ቅዳሴን በካሴት በቤት ውስጥ
ሆኖ ማስቀደስ ይገባል?” የሚለውን ጥያቄ ሲመልሱ እንዲህ
ይላሉ፡፡ “የቅዳሴ ዓላማው አንድ ነው፡፡ እሱም ቅዱስ
ሥጋውንና ክቡር ደሙን ፈትቶ ለምእመናን ማቅረብ ሲሆን
አባቶች እንደሚሉት ቅዳሴ የሕዝብ ነው፡፡ ሰዓታት
የሚባለውን የቤተ ክርስቲያን ጸሎት ካህናት ሲያደርሱ
ምእመናን ቢሳተፉበት በረከተ ሥጋና በረከተ ነፍስን
ያገኙበታል፡፡ ማኅሌት ሲቆም ኪዳን ሲደርስ ምእመናን ቢገኙ
በረከትን ያገኛሉ፡፡
ቅዳሴ ግን ለሕዝብ የሚፈጸም ሥርዐተ ጸሎት በመሆኑ
ቀዳስያኑ እና ምእመናኑ ፊት ለፊት እየተያዩ ሥጋ ወደሙን
ለመቀበል ደጅ ሲጠኑ ይታያሉ፡፡ ሥርዐተ ቅዳሴ ሲፈጸምም
በካህናትና በምእመናን ተሳትፎ ይከናወናል፡፡ ቴክኖሎጂው
በወለደልን ጥበብ ተጠቅሞ መዝሙርን ማዳመጥ ቅዳሴውን
መስማት ይቻላል፡፡የተቀረጸውን መስማት ብቻ ሳይሆን
ልንማርበትም እንችል ይሆናል፡፡ ከዚህ አልፎ የቤተ
ክርስቲያኑን ጸሎተ ቅዳሴ በካሴት በተቀረጸ ድምጽ ማስቀደስ
አይቻልም፡፡
በአሕዛብ አገር የሚኖሩ ሰዎች በአንድ የጸሎት ቤት
ተሰብስበው ቅዳሴ በቴፕ ያስቀድሱ እንደነበረ ሰምቻለሁ
እነዚህ ምእመናን ከቤታቸው ወጥተው መንገድ ሔደው
ቆመው ቅዳሴውን በቴፕ እየሰሙ “እትው በሰላም” /
በሰላም ወደቤታችሁ ግቡ/ ሲባሉ ይሰነባበታሉ፡፡ ይህ በጎ
አሳባቸውን እግዚአብሔር ተመልክቶ ቤተ ክርስቲያን
እንዲሠሩ ካህናቱም ቀድሰው እንዲያቆርቧቸው ረድቷቸዋል፡፡
የብሉይ ኪዳን ካህናት ያቀርቡት የነበረው መሥዋዕተ ኦሪት
ለሐዲስ ኪዳኑ (አማናዊው) መሥዋዕት ምሳሌ ሆኖ
እንዳደረሳቸው ከችግር አንጻር ቅዳሴን ለማስቀደስ ካላቸው
ልባዊ ፍላጎት ተነሣሥተው ያን ማድረጋቸው
አያስወቅሳቸውም፡፡ ያም ሆኖ ግን በመኖሪያ ቤታቸው
ሳይሆን ከቤታቸው ወጥተው መንገድ ተጉዘው የፈጸሙት
ተጋድሎ የሚበረታታ ነው፡፡ ይህ ሳይሆን ዝም ብሎ ተኝቶ
ቅዳሴን ሰምቶ አስቀድሻለሁ ማለት ድፍረት ነው፡፡ ቤተ
ክርስቲያን የቴክኖሎጂ ቅዳሴ የላትም ቅዳሴውም በምንም
ዐይነት መንገድ በቴፕ ድምጽ አይተካም፡፡ በአሁኑ ሰዓት ቤተ
ክርስቲያን ያልታነጸችበት ቦታ አለ ለማለት ትንሽ ያስቸግራል
ስለዚህ ቅዳሴን ማስቀደስ የሚገባው በቤተ ክርስቲያን
ተገኝቶ ነው”
መምህር ተስፋም በማያያዝ ምክራቸውን እንዲህ ሲሉ
አስተላልፈዋል፡፡ “ሊቀ ጠበብት የሰጡት አባታዊ ትምህርት
እንደተጠበቀ ነው፡፡ የተለየም ዐሳብ የለኝም ቅዳሴ
የሚቀደሰው በተቀደሰ ቦታ ነው፡፡ ይህ ማለት ታቦት ባለበት፣
ካህናት በተገኙበት፣ ውግረተ እጣን በሚደርስበት፣ ቡራኬ
በሚፈጸምበት ቅዱስ ቦታ ይከናወናል፡፡ በቅዳሴው ጊዜ እጣን
አለ፤ ጧፍ ይበራል፤ መሥዋዕት ይሰዋል፡፡ እነዚህ ነገሮች
ባልተሟሉበት ሁኔታ ቅዳሴን ማስቀደስ ፈጽሞ አይቻልም፡፡
ይህ ካልሆነ ቅዳሴው ቅዳሴ አይሆንም እላለሁ፡፡”
ማጠቃለያ
የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ሥርዐተ
እምነቷን ዶግማዋን እና ትውፊቷን ጠብቃ ጸሎተ ቅዳሴን
ታከናውናለች፡፡ ጸሎተ ቅዳሴ ተግባራዊ የሆነ አምልኮ
የምንፈጽምበት፣ መሠረታዊ እምነታችንን የምንገልጥበት
ወደ ምሥጢራተ ቤተ ክርስቲያን /ምሥጢረ ቊርባን/
የምንደርስበት በምድር ያለ ሰማያዊ ሥርዐት ነው፡፡ በዕለተ
ሰንበት በዐበይት በዓላት የሚቻለው አስቀድሶ ቅዱስ ሥጋውን
ክቡር ደሙን ይቀበላል፡፡ በንስሓ ራሱን ያላዘጋጀ ምእመን
ደግሞ አስቀድሶ ጠበል ጠጥቶ መስቀል ተሳልሞ ወደ ቤቱ
ይመለሳል፡፡
ሥርዐተ ቅዳሴ በካህናት መሪነት በዲያቆናት አስተናባሪነት
በምዕመናን ተሳትፎ በኅብረት የሚፈጸም ሥርዐት ነው፡፡
ሠራኢ ካህን ከመንበሩ በስተምዕራብ ቆሞ፣ ፊቱን ወደ
ምሥራቅ መልስ ንፍቁ ካህን ከመንበሩ በስተደቡብ ፊቱን ወደ
ሰሜን መልሶ፣ ሠራኢ ዲያቆኑ በስተምሥራቅ ፊቱን ወደ
ምዕራብ፣ ንፍቁ ዲያቆን በሰሜን ፊቱን ወደ ደቡብ በመቆም
መንበሩን ይከቡታል፡፡ አምስተኛው ልዑክም ከሠራኢው ካህን
በስተግራ ቆሞ ለካህኑ መብራት ያበራለታል፡፡ መጽሐፉ
በመንበር ላይ የሚቀመጥ ስለሆነ ሲገልጥ ጠሚችለው ንፍቁ
ቄስ ወይም ሌላ ቄስ ብቻ ነው፡፡ ይህ መደበኛ አቋቋማቸው
ሲሆን ሥርዐተ ቅዳሴው በሚከናወንበት ጊዜ ለቡራኬ
ለጸሎተ እጣን ለስግደት ከቦታ ወደ ቦታ ይንቀሳቀሳሉ፡፡
በቅኔ ማኅሌት በቅድስትና በመቅደስ ቆመው የሚያስቀድሱና
የሚያገለግሉ የምእመናን ወገንና ካህናት አሉ፡፡ በቅኔ
ማኅሌት በሰሜናዊ ምሥራቅ አቅጣጫ ያለ የአገልግሎት
ክፍል ወንዶች ምእመናን ቆመው ያስቀድሱበታል፡፡ በቅድስት
ምዕራባዊ ክፍል ቆሞሳት፣ ቀሳውስትና ዲያቆናት
ያስቀድሱበታል፡፡ በስተደቡብ በኩልም ደናግል መነኮሳይያት
የካህናት የዲያቆናት ሚስቶችና የሚቆርቡ ምእመናን ቆመው
ያስቀድሱበታል፡፡ በዚህ ክፍል ቆመው ያስቀደሱ ምእመናን
ሥርዐተ ቁርባን ይፈጽሙበታል፡፡ ይህ የቤተ መቅደሱ አሠራር
ቤተ ንጉሥ የሆነ እንዳልሆነ ነው፡፡ በመቅደሱ ክፍል ልኡካኑ
የሚቀድሱበት ሥጋ ወደሙ የሚፈትቱበት ካህናት ብቻ
የሚገቡበት ልዩ ቦታ ነው፡፡
በእነዚህ ቦታዎች ከላይ ያስቀመጥናቸውና ያልገለጥናቸው ልዩ
ልዩ አገልግሎቶች ይከናወኑበታል፡፡ ሥርዐተ ቅዳሴ ሲፈጸም
ካህናትና ምእመናን የድርሻቸውን ቃለ እግዚአብሔር
እየተቀባበሉ እየሰገዱ እየተባረኩ ሥርዐቱ ይከናወናል፡፡
ለዚህም ነው ሥርዐተ ቅዳሴ የሚታይ የሚዳሰስ የሚጨበጥ
የሚሰማ ክዋኔ አለው የምንለው፡፡ ቅዳሴን በካሴት
መስማት /ማዳመጥ/ ይቻል ይሆናል እንጂ ቡራኬ
የማስገኘት የምሥጢራት ተካፋይ የማድረግ እድል
አያሰጥም፡፡ በሥርዓተ ቤተ ክርስቲያንም እንደታደዘዘው ካህኑ
ቅዳሴን ከመጀመሩ በፊት ሊያስተውል ከሚገባው ጉዳዮች
አንዲ ምዕመናን መሰባሰባቸውን ማረጋገጥ ነው፡፡
የእግዚአብሔር ዐይኖች በቤተ መቅደስ ነው፡፡ ጆሮዎቹም
ወደ ምእመናን ጸሎት ነው፡፡ በመሆኑም እግዚአብሔር
ዐይኑንና ልቡን በመቅደሱ ሊያኖር ቃል ስለገባልን ወደ ቤተ
ክርስቲያን መሔድ የምሥጢራቱም ተካፋይ መሆን
ይጠበቅብናል፡፡ “በጎ እንደሆነ አውቆ ለማይሠራው ለዚያ
ሰው ኀጢአት ነው” ያዕ.4፥17 እንዳለው ሐዋርያው
ማስቀደስ ንስሓ መግባት ሥጋ ወደሙ መቀበል መልካም
ነገር ማድረግ በጎ እንደሆነ እያወቁ ያን አለመፈጸም ኀጢአት
ነው፡፡ “በዚህ ሥፍራ ለሚጸለይ ጸሎት ዐይኖቼ ይገለጣሉ፡፡
ጆሮቼም ያዳምጣሉ አሁንም ስሜ ለዘላለም በዚያ ይኖር
ዘንድ ይህን ቤት መርጫለሁ ቀድሻለሁም ዐይኖቼና ልቤም
ዘወትር በዚያ ይሆናል” 2ዜና.7፥15-17 ተብሎ እንደተጻፈ
ወደ ቤተ ክርስቲያን ሔደን የምንጸልየው ጸሎት
የምንፈጽመው ሥርዐተ አምልኮ በረከት የሚያሰጥ እንደሆነ
አምላካችን ነግሮናል፡፡ አበው ሐዋርያትም ጸሎትን በቤተ
መቅደስ በመገኘት ያደርጉ ነበር፡፡ “ጴጥሮስና ዮሐንስም
በዘጠኝ ሰዓት ለጸሎት በአንድነት ወደ ቤተ መቅደስ ወጡ፡፡
ሐዋ.3፥6 ስለዚህ በአንድነት ለጸሎት በቤተ ክርስቲያን
መሰብሰብ ሐዋርያት ትምህርት ነውና ልንፈጽመው ይገባል፡፡
ወስብሐት ለእግዚአብሔር

""ለቤተ ክርስቲያናችን ዛሬም ነገም እርስቷን ላናስነካ ቃልእንገባለን:: ቤተክርስቲያኔ ሆይ ብረሳሽ ቀኜ ትርወሳኝባላስብሽ ምላሴ ከትናጋዬ ይጣበቅ!!""
መስቀሉ የት ነው ያለው? ክፍል 1
ከዳንኤል ክብረት
በእምነት ታሪክ ውስጥ የታሪክ፣ የአርኬዎሎጂ እና
የቅርስ ጥናት ሰዎችን ያስጨነቁ ሁለት ጥያቄዎች አሉ፡፡
ታቦተ ጽዮን እና ጌታ የተሰቀለበት መስቀል የት ነው ያሉት?
የሚሉት ጥያቄዎች፡፡ እነዚህን ጥያቄዎች ለመመለስ
አሰሳዎች፣ ቁፋሮዎች፣ መዛግብትን የማመሳከር ሥራዎች፣
አሉ የተባሉ የይዞታ ጥያቄዎችን የመመርመር ፍተሻዎች
በመካሄድ ላይ ናቸው፡፡ በጣም የሚገርመው ነገር ግን
የዓለም ቅርሶች መናኸርያ የሆነችው ኢትዮጵያ ሁለቱንም
በተመለከተ ለዓለም የምትገልጣቸው ነገሮች አሏት፡፡
ሰሞኑን በሀገራችን ኢትዮጵያ የመስቀል በዓል
በመከበር ላይ በመሆኑ «ለመሆኑ ጌታ የተሰቀለበት መስቀል
የት ነው ያለው?» የሚለውን ጥያቄ በተመለከተ ያሉ
መረጃዎችን እንቃኝ፡፡
የመስቀሉ መጥፋት
በአብያተ ክርስቲያናት ከሚነገረው ትውፊት
በስተቀር ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ተሰቅሎት የነበረው
መስቀል እንዴት ሊጠፋ እንደቻለ የተመዘገበ ታሪክ እኔ
አላገኘሁም፡፡ አብዛኞቹ ጥንታውያን አብያተ ክርስቲያናት ግን
አይሁድ በመስቀሉ ላይ ይደረግ የነበረውን ተአምራት
በመቃወም ከክርስቲያኖች ነጥቀው እንደ ቀበሩት ይተርካሉ፡፡
የቤተ ክርስቲያን ታሪክ ጸሐፊው አውሳብዮስ የቆስጠንጢኖስ
የሕይወት ታሪክ /Life of Constantine/ በተሰኘው
መጽሐፉ ላይ በክርስቲያኖች ዘንድ ታላቅ ሥፍራ የነበረው
የጌታ መቃብር ተደፍኖ በላዩ ላይ የቬነስ ቤተ ጣዖት ተሠርቶ
እንደ ነበር ይናገራል፡፡ አውሳብዮስ በዝርዝር አይግለጠው
እንጂ ይህ የቬነስን ቤተ መቅደስ በጎልጎታ ላይ የመሥራቱ
ጉዳይ የሮሙ ንጉሥ ሐድርያን በ135 ዓም ኢየሩሳሌምን
Aelia Capitolina አድርጎ እንደ ገና ለመገንባት የነበረው
ዕቅድ አካል ነው፡፡
አይሁድ በሮማውያን ላይ እስከ ዐመጹበት እና ኢየሩሳሌም
ከክርስትና በኋላ ለመጀመርያ ጊዜ እስከ ጠፋችበት እስከ 70
ዓም ድረስ መስቀሉ በክርስቲያኖች እጅ እንደ ነበር
ይታመናል፡፡ በኋላ ግን ክርስቲያኖቹ የሮማውያንን እና
የአይሁድን ጦርነት በመሸሽ ከኢየሩሳሌም ወጥተው ወደ
ሌሎች ሀገሮች ሲሰደዱ፤ በኋላም በባር ኮባ ዐመፅ
ጊዜ /132-135 ዓም/ ኢየሩሳሌም ፈጽማ በሮማውያን
ስትደመሰስ የመስቀሉ እና የሌሎችም ክርስቲያናዊ ንዋያት
እና ቅርሶች ነገር በዚያው ተረስቶ ቀረ፡፡ ንጉሥ ሐድርያንም
የኢየሩሳሌም ከተማን ነባር መልክ በሚለውጥ ሁኔታ እንደ
ገና ሠራት፡፡ ያን ጊዜ ነው እንግዲህ የቬነስ ቤተ መቅደስ
በጌታችን መቃብር ላይ የተገነባው፡፡ ቆስጠንጢኖስ
ለኢየሩሳሌሙ ኤጲስ ቆጶስ ለአቡነ መቃርዮስ በጻፈው እና
ሶቅራጥስ እና አውሳብዮስ መዘግበው ባቆዩን ደብዳቤ ላይ
ይህ ታሪክ ተገልጧል፡፡
ቀጣዮቹ 300 ዓመታት ለክርስቲያኖች የመከራ
ጊዜያት ነበሩ፡፡ የሮም ቄሳሮች ክርስትናን እና ክርስቲያኖችን
የሚያሳድዱባቸው ዓመታት በመሆናቸው መስቀሉን የመፈለግ
ጉዳይ በልቡና እንጂ በተግባር ሊታሰብ አይችልም፡፡ ዓመታት
እያለፉ ሲሄዱም ኢየሩሳሌም እየተዘበራረቀች እና የጥንት
መልኳ እየተቀየረ በመሄዱ በጌታ መቃብር ላይም የሮማ
አማልክትን ለማክበር ቤተ መቅደስ በመሠራቱ ነገሩ ሁሉ
አስቸጋሪ እየሆነ ሄደ፡፡
የመስቀሉ እንደገና መገኘት
ጥንታውያን የቤተ ክርስቲያን ታሪክ ጸሐፊዎች
መስቀሉን እንደገና ያገኘችው ንግሥት ዕሌኒ መሆንዋን
ይናገራሉ፡፡ በ380 ዓም አካባቢ የተወለደው ታሪክ ጸሐፊው
ሶቅራጥስ Ecclesiastical History በተሰኘው መጽሐፉ
ላይ በምእራፍ 17 መስቀሉ እንዴት እንደ ተገኘ ዝርዝር
መረጃ ይሰጠናል፡፡ ንግሥት ዕሌኒ ወደ ኢየሩሳሌም ተጉዛ
በጎልጎታ የጌታ መቃብር ላይ የተሠራውን የቬነስ ቤተ
መቅደስ አፈረሰችው፤ ቦታውንም በሚገባ አስጠረገችው፡፡
በዚያን ጊዜም የጌታችን እና የሁለቱ ሽፍቶች መስቀሎች
ተገኙ፡፡ ከመስቀ ሎቹም ጋር ጲላጦስ የጻፈው የራስጌው
መግለጫ አብሮ ተገኘ፡፡
ሶቅራጥስ ከሦስቱ መስቀሎች አንዱ የክርስቶስ መሆኑን
እንዴት ሊታወቅ እንደቻለ ሲገልጥ እንዲህ ይላል «አቡነ
መቃርዮስ በማይድን በሽታ ተይዛ ልትሞት የደረሰችን አንዲት
የተከበረች ሴት አመጡ፡፡ ሁለቱን መስቀሎችንም አስነኳት፤
ነገር ግን ልትድን አልቻለችም፤ በመጨረሻ ሦስተኛውን
መስቀል ስትነካ ድና እና በርትታ ተነሣች፡፡ በዚህም የጌታ
መስቀል የትኛው እንደሆነ ታወቀ» ይላል፡፡ ከዚያም ንግሥት
ዕሌኒ በጌታ መቃብር ላይ ቤተ ክርስቲያን አሠራች፡፡
ከመስቀሉ የተወሰነውን ክፍል ከፍላ ከችንካሮቹ ጋር ወደ
ቁስጥንጥንያ ስትወስደው ዋናውን ክፍል በጎልጎታ ቤተ
ክርስቲያን ተወችው፡፡
ይህንን ታሪክ ሄርምያስ ሶዞሜን የተባለው እና
በ450 ዓም አካባቢ ያረፈው ታሪክ ጸሐፊም Ecclesiastical
History, በተሰኘው ጥንታዊ መጽሐፉ በክፍል ሁለት ምእራፍ
አንድ ላይ ይተርከዋል፡፡ ዞሲማን እንደሚለው በ325 ዓም
የተደረገው ጉባኤ ኒቂያ ሲጠናቀቅ የቆስጠንጢኖስ ትኩረት
ወደ ኢየሩሳሌም ዞረ፡፡
ምንም እንኳን ሶዞሜን ባይቀበለውም መስቀሉ
የተቀበረበትን ቦታ ያመለከተው ከከተማዋ በስተ ምሥራቅ
ይኖር የነበረ አንድ አይሁዳዊ መሆኑን እና እርሱም ይህንን
መረጃ ከትውልድ ወደ ትውልድ ሲተላለፍ ከነበረ መዝገብ
ማግኘቱን እንደ ሰማ ጽፏል፡፡ ንግሥት ዕሌኒ ባደረገችው
አስቸጋሪ ቁፋሮ መጀመርያ ጌታ የተቀበረበት ዋሻ፤ ቀጥሎም
ከእርሱ እልፍ ብሎ ሦስቱ መስቀሎች መገኘታቸውን ሶዞሜን
ይተርካል፡፡ ከመስቀሎቹም ጋር የጲላጦስ ጽሑፍ አብሮ
መገኘቱን እና የጌታ መስቀል ከሌሎች የተለየበትን ሁኔታ
ከሶቅራጥስ ጋር ተመሳሳይ በሆነ ሁኔታ ይተርከዋል፡፡
ንግሥት ዕሌኒ በጎልጎታ፣ በቤተልሔም፣ በደብረ
ዘይት፣ አብያተ ክርስቲያናትን አሠርታ በሰማንያ ዓመቷ
እንዳረፈች ሶዞሜን ይተርካል፡፡ ብዙ የታክ ጸሐፊዎች
ዕረፍቷን በ328 ዓም አካባቢ መስቀሉ የተገኘ በትንም
በ326 ዓም ያደርጉታል፡፡
በ457 ዓም አካባቢ ያረፈው ቴዎዶሮት የተባለው
ታሪክ ጸሐፊም የመስቀሉን የመገኘት ታሪክ ተመሳሳይ በሆነ
መንገድ ያቀርበዋል፡፡
መስቀሉ በኢየሩሳሌም
ንግሥት ዕሌኒ ለበረከት ያህል የተወሰነ ክፍል ወደ
ቁስጥንጥንያ ከመውሰዷ በቀር አብዛኛውን የመስቀሉን ክፍል
በብር በተሠራ መሸፈኛ አድርጋ በጎልጎታ ቤተ ክርስቲያን
እንዲቀመጥ ለአቡነ መቃርዮስ ሰጥታቸዋለች፡፡ ይህ መስቀል
በየተወሰነ ጊዜ እየወጣ ለምእመናኑ ይታይ እንደ ነበር
አንዳንድ መረጃዎች ያመለክታሉ፡፡ በ380 ዓም ኤገርያ
የተባለች ተሳላሚ መነኩሲት ቅዱስ መስቀሉ ወጥቶ
በተከበረበት በዓል ላይ ተገኝታ ያየችውን ለመጣችበት ገዳም
ጽፋ ነበር፡፡ /M.L. McClure and C. L. Feltoe, ed. and
trans. The Pilgrimage of Etheria, Society for
Promoting Christian Knowledge, London,
(1919)/
አንዳንድ መረጃዎች እንደሚጠቁሙት የመስቀሉ
ክፍልፋዮች ወደ ተለያዩ ሀገሮች መወሰድ የጀመሩት በዚህ ጊዜ
ነው፡፡ በሞሪታንያ ቲክስተር በተባለ ቦታ የተገኘውና በ359
ዓም አካባቢ የተጻፈው መረጃ የመስቀሉ ክፍልፋዮች ቀደም
ብለው ወደ ሌሎች ሀገሮች መግባት እንደ ጀመሩ ያሳያል፡፡
ቄርሎስ ዘኢየሩሳሌም መስቀሉ ከተገኘ ከሃያ አምስት
ዓመታት በኋላ በ348 ዓም በጻፈው አንድ ጽሑፍ ላይ «ዓለሙ
በሙሉ በጌታችን መስቀል ክፍልፋዮች ተሞልቷል» በማለት
ገልጦ ነበር፡፡ ከዚህም ጋር «ዕጸ መስቀሉ እየመሰከረ ነው፡፡
እስከ ዘመናችንም ድረስ ይኼው እየታየ ነው፡፡ ከዚህ
ተነሥቶም በመላው ዓለም እየተሠራጨ ነው፡፡ በእምነት
ክፍልፋዮቹን እየያዙ በሚሄዱ ሰዎች አማካኝነት» ብሏል፡፡/
On the Ten Points of Doctrine, Colossians II.
8./
ዮሐንስ አፈ ወርቅም የመስቀሉን ቅንጣቶች ሰዎች
በወርቅ በተሠራ መስቀል ውስጥ በማድረግ ምእመናን
በአንገታቸው ላይ ያሥሩት እንደ ነበር ጽፏል፡፡ በዛሬዋ
አልጄርያ በቁፋሮ የተገኙ ሁለት ጽሑፎች የመስቀሉ
ክፍልፋዮች በ4ኛው መክዘ የነበራቸውን ክብር ይናገራሉ፡፡ /
Duval, Yvette, Loca sanctorum Africae, Rome
1982, p.331-337 and 351-353/፡፡ በ455 ዓም
በኢየሩሳሌም የነበረው ፓትርያርክ ለሮሙ ፖፕ ለልዮን
የመስቀሉን ቁራጭ እንደ ላከለት ተመዝግቧል፡፡
በአውሮፓ ምድር የተዳረሰው አብዛኛው የመስቀሉ
ክፍልፋይ የተገኘው ከባዛንታይን ነው፡፡ በ1204 ዓም
በአራተኛው የመስቀል ጦርነት ጊዜ የዘመቻው ተካፋዮች
በዓረቦች ጦር ድል ሲመቱ ፊታቸውን ወደ ቁስጥንጥንያ
አዙረው ከተማዋን፣ አድባራቱን እና ገዳማቱን ዘረፏቸው፡፡
በዚያ ጊዜ ተዘርፈው ከሄዱት ሀብቶች አንዱ ዕሌኒ
ከኢየሩሳሌም ያመጣችው የመስቀሉ ግማድ ነበር፡፡ ይህንን
ግማድ እንደ ገና በመከፋፈል አብዛኞቹ የአውሮፓ አብያተ
ክርስቲያናት ሊዳረሱት ችለዋል፡፡ የወቅቱን ታሪክ ከመዘገቡት
አንዱ ሮበርት ዲ ክላሪ «በቤተ መቅደሱ ውስጥ አያሌ ውድ
ንዋያት ይገኙ ነበር፡፡ ከእነዚህም መካከል ከጌታ መስቀል
የተቆረጡ ሁለት ግማዶች ነበሩ፡፡ ውፍረታቸው የሰው እግር
ያህላል፤ ቁመታቸውም ስድስት ጫማ ይህል ነበር»
ብሏል፡፡ /Robert of Clari's account of the
Fourth Crusade, chapter 82: OF THE MARVELS
OF CONSTANTINOPLE/
የመስቀሉ ለሁለተኛ ጊዜ መጥፋት
እስከ ስድስተኛው መክዘ ድረስ በኢየሩሳሌም ጎልጎታ
የነበረው መስቀል በ614 ዓም በፋርሱ ንጉሥ ክሮስረስ 2ኛ /
Chrosroes II/ ተወሰደ፡፡ የፋርሱ ንጉስ ኢየሩሳሌምን
በወረረ መስቀሉን እና ፓትርያርክ ዘካርያስን ማርኮ ወደ ፋርስ
ወሰዳቸው፡፡ እንደ ገና ወደ ኢየሩሳሌም የተመለሰው ሕርቃል
በ627 ዓም ባደረገው ጦርነት ክሮስረስ ድል ሲሆን ነው፡፡
ሕርቃል በመጀመርያ ወደ ቁስጥንጥንያ ካመጣው በኋላ እንደ
ገና ወደ ኢየሩሳሌም ወስዶ በቀድሞ ቦታው በጎልጎታ
አስቀምጦት ነበር፡፡
እስከ አሥረኛው መክዘ ድረስ በኢየሩሳሌም
በቀድሞ ክብሩ ቢቆይም ዐረቦች አካባቢውን እየተቆጣጠሩ
ሲመጡ በኢየሩሳሌም የሚኖሩት ክርስቲያኖች መስቀሉን
በ1009 ዓም አካባቢ ሠወሩት፡፡ ለ90 ዓመታት ያህል ያለበት
ቦታ ተሠውሮ ከኖረ በኋላ በመጀመርያው የመስቀል ጦርነት
ጊዜ በ1099 ዓም ከተሠወረበት ወጥቶ እንደ ቀድሞው
መታየት ጀመረ፡፡
ለሦስተኛ ጊዜ መጥፋት
በ1187 ዓም በሐቲን ዐውደ ውጊያ ሳላሕዲን
የተባለው የዓረቦች የጦር መሪ የመስቀል ጦረኞችን ድል
አድርጎ ኢየሩሳሌምን ሲቆጣጠር በዚያ የነበረውን መስቀል
መውሰዱን አንዳንድ የታሪክ መዛግብት ይገልጣሉ፡፡ ከዚያ
በኋላ ግን መስቀሉ የት እንዳለ እስካሁን ማረጋገጥ
አልተቻለም፡፡ በወቅቱ የነበሩት የሮም ነገሥታት መስቀሉን
ለማግኘት ከሳላሕዲን ጋር ብዙ ድርድር አድርገው
ሳይሳካላቸው ቀርቷል፡፡
በአብዛኞቹ ጥንታውያን አብያተ ክርስቲያናት ዘንድ
የመስቀሉ ክፍልፋይ እንዳለ ሁሉም ይናገራሉ፡፡ አንዳንዶቹ አለ
የሚባለው ክፍልፋይ ከመብዛቱ የተነሣ የሚያነሡት ትችት
አለ፡፡ ጆን ካልቪን «ሁሉም ክፍልፋዮች ከመስቀሉ የወጡ
ከሆነ፤ እነዚህን ሁሉ ብናሰባስባቸው አንድ መርከብ የግድ
ያስፈልጋቸዋል፡፡ ወንጌል ግን ይህንን መስቀል አንድ ሰው
እንደ ተሸከመው ይነግረናል» ብሎ ነበር፡፡
ይህንን የካልቪንን ሂስ በተመለከተ መልስ የሰጠው
ራውል ዲ ፈሌውሪ /Rohault de Fleury,/ በ1870 ዓም
በዓለም ላይ አሉ በሚባሉት የመስቀል ክፍልፋዮች ላይ ጥናት
አድርጎ ነበር፡፡ ራውል መጀመርያ የት ምን ያህል መጠን
እንዳለ ካታሎግ አዘጋጀ፤ ከዚያም መጠናቸውን አንድ ላይ
ደመረ፡፡ በታሪክ እንደሚነገረው የመስቀሉ ክብደት 75 ኪሎ፣
ጠቅላላ መጠኑም 178 ኪዩቢክ ሜትር ነው፡፡ ራውል
ያገኛቸውና አሉ የተባሉት ክፍልፋዮች አንድ ላይ
ቢደመሩ .004 ኪዩቢክ ሜትር /3.‚942‚000 ኪዩቢክ ሚሊ
ሜትር/ ነው፡፡ በዚህም መሠረት ቀሪው 174 ኪዩቢክ
የሚያህለው ሜትር የመስቀሉ ክፍል ጠፍቷል ማለት ነው
ብሏል፡፡ /Mémoire sur les instruments de la
Passion, 1870/
ግማደ መስቀሉ በኢትዮጵያ
የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ቤተ ክርስቲያን መዛግብት
እንደሚሉት ግማደ መስቀሉ ወደ ኢትዮጵያ የገባው በ14ኛው
መክዘ በዐፄ ዳዊት ዘመነ መንግሥት ነው፡፡ በግሼን አምባ
የተቀመጠው ደግሞ በዐፄ ዘርዐ ያዕቆብ ዘመነ መንግሥት
ነው፡፡
ኢትዮጵያውያን ወደ ኢየሩሳሌም ያደርጉ የነበረውን
ጉዞ፣ የኢትዮጵያ ነገሥታት የነበራቸውን ታዋቂነት እና ወደ
ሀገረ ናግራን ተጉዘው የሠሩትን ሥራ ስንመለከት ኢትዮጵያ
እስከዚያ ዘመን ድረስ ግማደ መስቀሉን ለማግኘት ትዘገያለች
ብሎ ለማሰብ ይከብዳል፡፡ በኢየሩሳሌም የሚገኘው
የኢትዮጵያ ገዳም መስቀሉ ለወጣበት ቦታ እና ለጎልጎታ
ያለውን ቅርበት፤ ዐፄ ካሌብም ከናግራን ዘመቻ በኋላ
ዘውዳቸውን ለጎልጎታ ቤተ ክርስቲያን መላካቸውን ስናይ
ይህንን የመሰለ ቅዱስ ንዋይ ኢትዮጵያውያን እስከ 13ኛው
መክዘ ድረስ አንዱን ክፋይ ሳያገኙት ቆዩ ለማለት ያስቸግራል፡፡
ኤርትራ ውስጥ ግማደ መስቀሉ አለበት የሚባል አንድ ገዳም
መኖሩን ሰምቻለሁ፡፡
ክርስትና ብሔራዊ ሃይማኖት ከሆነ በኋላ ነገሥታቱ
በሳንቲሞቻቸው ላይ የመስቀል ምልክት ማድረጋቸው፣ እንደ
ንጉሥ አርማሕ ያሉትም በበትረ መንግሥታቸው ላይ መስቀል
ማድረጋቸው፤ ከቀደምት ክርስቲያን ነገሥታት አንዱ የሆነው
ንጉሥ ዐፄ ገብረ መስቀል ተብሎ መሰየሙን ስናይ የመስቀሉ
ነገር በኢትዮጵያ ውስጥ የነበረውን ቀደ ምት ታሪክ
ያመለክተናል፡፡
በዛግዌ ሥርወ መንግሥትም ዐፄ ላሊበላ ስመ
መንግሥቱ ገብረ መስቀል መባሉን፣ ሚስቱም ንግሥት
መስቀል ክብራ መባሏን፣ ከሠራቸው አስደናቂ ውቅር አብያተ
ክርስቲያ ናት አንዱ ቤተጊዮርጊስ በመስቀል ቅርጽ
መሠራቱን ስናይ ኢትዮጵያውያን ከመስቀሉ ጋር ቀድመው
መተዋወቃቸውን ያስገምተናል፡፡ በመሆኑም በዚህ ረገድ
መዛግብትን የማገላበጥ እና የመመርመር ሥራ የሚቀረን
ይመስላል፡፡
በዐፄ ዳዊት ዘመን መጥቶ በዐፄ ዘርዐ ያዕቆብ
አማካኝነት በግሼን አምባ የተቀመጠው ግማደ መስቀል
በይፋ የታወቀውና በነገሥታቱ ዲፕሎማሲያዊ ጥረት የመጣው
ዋናው እንጂ የመጀመርያው ነው ለማለት ያስቸግራል፡፡
ተክለ ጻድቅ መኩርያ ግብጻዊው ጸሐፊ ማክሪዝ
Historia Rerum Isi amiticarumin Abissinia
በሚለው መጽሐፉ የገለጠውን መሠረት በማድረግ
«የኢትዮጵያ ታሪክ ከይኩኖ አምላክ እስከ ልብነ ድንግል»
በሚለው መጽሐፋቸው ላይ እንደሚተርኩት አስቀድሞ በሰይፈ
አርእድ ዘመን በግብጹ ሡልጣን እና በኢትዮጵያዊው ንጉሥ
መካከል የተፈጠረውን ችግር ለመፍታት የልዑካን ቡድን ወደ
ኢትዮጵያ መጥቶ ነበር፡፡ የልዑካን ቡድኑ መሪ የኢየሩሳሌሙ
ፓትርያርክ አባ ዮሐንስ ነበሩ፡፡
ልዑካኑ ወደ ኢትዮጵያ ሲደርሱ ያገኟቸው ዐፄ
ዳዊትን ነበር፡፡ በሁለቱ ሀገሮች መካከል የነበረውን ችግር
በውይይት እና በስምምነት ፈትተው አስማሟቸው፡፡ ዐፄ
ዳዊትም ግማደ መስቀሉን እንዲልኩለት የኢየሩሳሌሙን
ፓትርያርክ አቡነ ዮሐንስን አደራ አላቸው፡፡ እርሳቸውም
ከግማደ መስቀሉ ጋር ሌሎች ንዋያትንም ጨምረው
ላኩለት፡፡ በግብጹ ሡልጣን እና በንጉሥ ዳዊት መካከል
የተፈጸመው ስምምነት ለኢትዮጵያውያን ተሳላሚዎች እና
ነጋዴዎች ጥበቃ ማድረግን የሚያካትት ስለ ነበር ግማደ
መስቀሉን የያዙት የዐፄ ዳዊት መልእክተኞች ያለ ችግር
ኢትዮጵያ ገቡ፡፡
አንዳንድ የታሪክ መዛግብት ዐፄ ዳዊት ጥቅምት
ዘጠኝ ቀን 1404 ዓም በድንገት ሲያርፉ ግማደ መስቀሉ
በሱዳን ስናር ነበር ይላሉ፡፡ ከስናር ያነሡት ዐፄ ዘርዐ ያዕቆብ
መሆናቸውንም ይተርካሉ፡፡ ተክለ ጻደቅ መኩርያ ግን ዐፄ
ዳዊት ወደ ኢትዮጵያ አስገብተውት በተጉለት ውስጥ ቤተ
ክርስቲያን ሠርተውለት እንደ ነበር ይናገራሉ፡፡ ዐፄ ዘርዐ
ያዕቆብ የነገሡት በ1434 ዓም ነው፡፡ በእነዚህ ሠላሳ
ዓመታትም አያሌ ነገሥታት ተፈራርቀዋል፡፡ እነዚህ ነገሥታት
ግማደ መስቀሉን ለመውሰድ ያልቻሉበትን ምክንያት ማወቅ
አይቻልም፡፡ ምናልባት ግን በነበረው የርስ በርስ ሽኩቻ
ተጠምደው ይሆናል፡፡ ሌሎች መዛግብት እንጂ በኋላ ዘመን /
ምናልባትም በዐፄ ልብነ ድንግል/ የተጻፈው የዐፄ ዘርዐ
ያዕቆብ ዜና መዋዕል የግማደ መስቀሉን ነገር አይነግረንም፡፡
ዐፄ ዘርዐ ያዕቆብ ግሼን አምባ ላይ ግማደ
መስቀሉን ያስቀመጠበት ሁለት ምክንያቶች ይኖራሉ፡፡
የመጀመርያው የአምባው የመስቀለኛ ምልክት ሲሆን
ሁለተኛው ደግሞ አምባው በዘመኑ በልዩ የንጉሠ ነገሥቱ
ኃይል ይጠበቅ ስለ ነበር ነው፡፡ በግራኝ አሕመድ ወረራ ጊዜም
ቢሆን ሌሎች ሀብቶች ከአምባው ላይ መዘረፋቸውን እንጂ
የተቀበረውን ለማውጣት ሙከራ መደረጉን የግራኝን ታሪክ
የጻፈው ዐረብ ፋቂህ አያነሣም፡፡
ግማደ መስቀሉን የማውጣት ጥረት ተደረገ
የሚባለው በ1851 ዓም ዐፄ ቴዎድሮስ በጣም የሚወዷቸው
ባለቤታቸው እቴጌ ምንትዋብ ከሞቱ ከአንድ ዓመት በኋላ
ነው፡፡ ንጉሥ ቴዎድሮስ እቴጌ ምንትዋብን እጅግ ይወዷቸው
ስለነበር በመስቀሉ አማካኝነት ከሞት ለማስነሣት አስበው
ነበር፡፡ ይህንንም በወታደሮች ኃይል በማስቆፈር
አስጀምረውት ነበር፡፡ በመካከል ግን ከጉድጓዱ ኃይለኛ ሽታ
እና ጢስ ወጥቶ ከቆፋሪዎቹ የተወሰኑትን በመግደሉ
ሃሳባቸውን ሠርዘው ባለቤታቸውን በግሼን አምባ ቀብረው
ተመልሰዋል፡፡

""ለቤተ ክርስቲያናችን ዛሬም ነገም እርስቷን ላናስነካ ቃልእንገባለን:: ቤተክርስቲያኔ ሆይ ብረሳሽ ቀኜ ትርወሳኝባላስብሽ ምላሴ ከትናጋዬ ይጣበቅ!!""

Tuesday, 18 September 2012

kidus yared:::;

ሊቁ ቅዱስ ያሬድ ዜማውና 1500ኛ አመት መታሰቢያ ክፍል
አንድ
ቅዱስ ያሬድ ከአባቱ ከአብዩድ /ይስሐቅ/ ከእናቱ ከክርስቲና /
ታውካልያ/ በ505 ዓ.ም. ሚያዚያ 5 ቀን በአክሱም
ተወለደ፡፡ በዚህም መሰረት ታላቁ ቅዱስ ያሬድ በሚመጣው
ሚያዝያ አምስት 1500 ዓመት ይሆነዋል ማለት ነው
፡፡ ታዲያ የዚህ ታላቅ አባት ለኢትዮጵያ እና ለቤተ
ክርስቲያናችን ካበረከተው ታላቅ የአለም ሀብት አንፃር
1500ኛ አመቱ በታላቅ ድምቀት አመቱን ሙሉ መታሰብ
ይኖርበታል ፡፡
መቼም ቢሆን እንዲት ሃገር የራሷ የሆነው ባህሏ /
ሥርዓቷ/ የሚያኮራትና ማንነቷንም የሚያንጸባርቅ በመሆኑ
ልትጠብቀውና ከትወልድ ወደ ትውልድ ልታስተላልፈው
የባለቤትነት ግዴታዋ ነው ፡፡
በመሆኑም
ሀገራችን ኢትዮጵያን ለጥቁር ሕዝቦች መኩሪያ እንድትሆን
ያደረጋት የልጆቿ ሀገር ወዳድነትና ጀግንነትን የተመላው ባህሏ
ብቻ ሳይሆን የሃይማኖት፣ የሥነ ዜማ ሀገር መሆኗም
መጻሕፍተ ታሪክን ባነበቡ ሊቃውንት አንደበት ብቻ ሳይሆን
በማዳመጥ ትውፊት /ርክክብ/ ለኅብረተሰቡ ኀቡእ ያልሆነ
ነገር መሆኑ ነው ፡፡
በተጨማሪም ሀገራችን ኢትዮጵያ የዘመናት ዑደት
ስፍር ቀምር የራሷን ዜማ ያደላደለች አፍሪካዊት እመቤት
ናት ብንል ጽልመት ሊጋርደው የማይችለው ገሀድ ነው፡፡
ይሁን እንጂ እኛ ልጆቿ የትናንቱን ለዛሬ ትውልድ ማበርከት
ያልቻልን ይመስላል ፡፡ ለዚህም ነው ትናንት የተነሱ የዜማ
ሊቃውንት እነ ሞዛርት ከቅዱስ ያሬድ 1250 ዓመት ብኋላ
የተወለዱት በዓለም የዜማ ሊቃውንት ሲባሉ ቀደምት
የሆነው ቅዱስ ያሬድ ግን ኢትዮጵያውያን እንኳን ስራውን
እንዳንዘክረው ስራዎቹን ተራ ስራ ተደርገው እንዲታዩ
የማይፈነቀል ድንጋይ የለም፡፡
አበው ለብዙ ዘመናት ይህን ዜማ በዜማ ቤቱ፣
በቅኔ ቤቱ በመጻሕፍት ቤቱ እንዳልተጠቀሙበት ሁሉ ዛሬ
ግን የአበው ያለህ ብለን ቅዳሴውን በንባብና በአማረኛ
ለውጠን ዜማው እነዲዘነጋ ከፍተኛ አስተዋፅኦ እያደረግን
ነው፡፡ ይህ ግን “የቆጡን አወርድ ብላ የብብቷን ጣለች”
ሳያሠኝ አይቀርም ፡፡
ቢቻል ቀደምት የዜማ ምልክት ደራሲ መሆኑንም ጭምር
ቤተ ክርስቲያን ለአለም የምታሳውቅበት ጊዜ ቢኖር ይህ
ይመስለኛል ለዚህ የተቀደሰ ተግባር ደግሞ እያንዳንዳችን
ከዛሬ ጀምረን በየአጥቢያችን ታላላቅ በአላትን ተንተርሰን
የሚዘከርበትን ሁኔታዎችን መፍጠር ይገባል ከመስቀል በዓል
አከባበር ቢጀምር ባዮች ነን፡፡ በረከቱ ሁሌም አይለየን፡፡
ስራ ምግባር ባይኖረን የቅዱሳንን መንፈሳዊ
ተጋድሎ ማውሳት መዘከርም ታላቅ ስጦታ ነው :: መንፈሳዊ
ተጋድሎ የክርስቲያኖች ህይወት ለታላቅ ክብር የሚያበቃ
በመሆኑ ወደ እግዚአብሔር የምንቀርብበትን እና
ለእግዚአብሔር የምንገዛበትን መንፈሳዊ ተጋድሎ ነው፡፡
ይኸውም ስለ ቅዱሳንን አባቶቻችን ተጋድሎ ማውሳት
ለመንፈሳዊነታችን ታላቅ አስተዋፅኦ አለው፡፡ በየዕለቱ
የምንሰማው የቅዱሳን ሕይወትና ታሪክ እነርሱ ወደ
ተጋደሉበት የቅድስና መንገድ የሚመራንና ለተሻለ የመንፈሳዊ
ህይወት የምንገጓዝበት ትልቅ ድልድይ ነው፡፡ ያዕ 9፣7 .መዝ
72፣28
‘’ሰይጣን ራሱ የብርሃን መልአክ እንዲመስል ራሱን ይለውጣል
‘’ 2ኛ ቆሮ 11፣14 ቅዱሳን ሁሉ ይህን የሰይጣን ተንኮል
ፍጹም በመንፈስ ቅዱስ ተቃኝተው የራሳቸው አገልጋይ
እስከማድረግ ደረጃ ደርሰዋል፣መሬት ተከፍታ
እንድትውጠውም አድርገዋል፡፡ የዚህ ሁሉ ጸጋ ሰጪ ባለቤቱ
መድኃን ዓለም ኢየሱስ ክርስቶስ ነው፡፡ስለዚህም ቅዱሳንን
መሳደብ የክብር ጌታን መሳደብ ነውና አውሬው ራዕ 13፣6
ከዚህ ምግባሩ ሊጠነቀቅ ይገባል፡፡ ’በዓለም ግን መከራ
ትቀበላላችሁ ነገር ግን ጽኑ እኔ ዓለምን ድል ነስቼዋለሁ ‘’ዮሐ
16፣33 ለነቢያት፣ ለሐዋሪያት፣ ለአበው ቅዱሳን እና
ለቅዱሳን እናቶቻችን የተሰጠውን የእግዚአብሔርን ጸጋ
ለማግኘትና ዲያብሎስን ድል ለማድረግ በጾም ፣በጸሎት ፈቃደ
እግዚአብሔር የሆነውን ሁሉ በመፈጸም መልካሙን
የእምነት ገድል ፈጽመን የመጽሐፍ ቅዱስን ቃል መሰረት
አድርገን ሃይማኖታችንን እስከ ሞት ድረስ ታምነን
እንድንጠብቅ የቅዱሳን አምላክ ይርዳን::
ወደ ቀደመ ነገራችን ስንመለስ ቅዱስ ያሬድ በተወለደ በሰባት
ዓመቱ አባቱ ስለሞተ እናቱ ክርስቲና የአክሱም ገበዝ ለነበረው
ለአጐቱ ለጌዴዎን እንዲያሳድገውና እንዲያስተምረው
ሰጠችው፡፡ ትምህርት አልዋሃድ ስላለውና ቁጣውና አለንጋው
ስለበዛበት ጠፍቶ ማይኪራህ ወደምትባል ቦታ በመሰደድ
በአንዲት ዛፍ ሥር አርፎ እያለቀሰ ሳለ አንድ ትል አየ፡፡ ትሉም
ለ6 ጊዜያት በዛፉ ላይ እወጣለሁ እያለ ሲወድቅ፤ በሰባተኛው
ግን ከዛፉ ላይ ወጥቶ የዛፉን ፍሬ ሲበላ አየ፡፡ ቅዱስ ያሬድም
ተስፋ አለመቁረጥን እግዚአብሔር ካዘጋጀለት ትል ተምሮና
ወደ ልቡ ተመልሶ ወደ አጎቱ መጥቶ ይቅርታ በመጠየቅ
ትምህርቱን ቀጠለ፡፡ ብልህ ሰው በጥቂት ነገር ይማራል፡፡
እግዚአብሔርም ገለጠለትና በሚገባ ተማረ፡፡
እግዚአብሔርም በቅዱስ ያሬድ መመስገንን በወደደ ጊዜም
ከኤዶም ገነት ሦስት አእዋፋትን በመላክ እግዚአብሔር ወደ
ሰማይ ጠራው፡፡ እርሱም ወደ ሰማይ ተነጥቆ 24ቱ ካህናተ
ሰማይ ሲያመሰግኑ ሰምቶ አይቶ ተመለሰ፡፡ ወዲያውም ከጧቱ
በ3 ሰዓት በአክሱም ቤተክርስቲያን በታቦተ ፅዮን ፊት ቆሞ
«ሃሌ ሉያ ለአብ፣ ሃሌ ሉያ ለወልድ፣ ሃሌ ሉያ ለመንፈስ ቅዱስ
ቀዳሚሃ ለጽዮን ሰማየ ሣረረ ወበዳግም አርአዮ ለሙሴ
ዘከመ ይገብር ግብራ ለደብተራ» ብሎ በልሣነ ግእዝ ዘመረ
የዜማውም ስልት አራራይ ነበር፡፡ ትርጓሜውም «ለአብ
ምሥጋና ይገባል፣ ለወልድም ምስጋና ይገባል፤ ለመንፈስ
ቅዱስም ምስጋና ይገባል ከጽዮን አስቀድሞ እግዚአብሔር
ሰማይን ፈጠረ ዳግመኛም ለሙሴ የድንኳኑን ሥራ አሳየ»
ማለት ነው፡፡ ይህችን ዜማ ቅዱስ ያሬድ «አርያም» አላት፤
ከመላእክት ወይም ከሰማይ የተገኘች ማለት ነው፡፡ ከዚህ
በኋላ የተለያዩ ዜማዎችን ደርሷል፡፡
የቅዱስ ያሬድ የስሙም ትርጓሜ ብዙ ነው፡፡ ያሬድ ማለት
«ራዕየ ምሥጢር፣ ነፃሬ ኅቡአት» ማለት ነው፤ የመላእክት
ምስጢር የነበረውን ጸዋተወ ዜማ አምልቶና አስፍቶ
በመናገሩ፡፡ አንድም ያሬድ ማለት «ንብ» ማለት ነው፤ ንብ
የማይቀስመው አበባ እንደሌለ ሁሉ ያሬድም ከመጻሕፍት
የማይጠቅሰው የለምና፡፡ በንቡ የተቀሰመው ማር እጅግ
ጣፋጭ ከመሆኑም በላይ ሰሙ ለመብራት ውሎ ጨለማን
አርቆ ብርሃንን እንደሚሰጥ ሁሉ፤ የቅዱስ ያሬድም ዜማ
ንባቡ ከምሥጢሩ ጋር ተዋሕዶ ምእመናንን ደስ ከማሰኘቱም
በላይ መናፍቃንን የሚያሳፍር ለምእመናን ተድላ ደስታን
የሚያበስር ፣ ኃይለ ቃሉ እንደ መብረቅ የሚያንጸባርቅ ፣
ጨለማ ክህደትን የሚያርቅ ፣ ብርሃነ ጥበብ የተመላበት
ነው፡፡
ይቆየን…….ይቀጥላል ከአንድ ቀን ብኋላ ቀጣዩን ክፍል
እናቀርባለን::
የቅዱስ ያሬድ በረከት ረድኤት አይለየን፡፡ አሜን::
from dekike nabute blog
ማኖታውያን መስለው ከሚመጡ
መናፍቃን ተጠንቀቁ ማቴ 7፥15
መስከረም 8 ቀን 2005 ዓ.ም.
አባ ዘሚካኤል
የተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ለዘመናት ያቆየችውን ትውፊት፣
ቅርስና ሀብት፣ ቋንቋና ዜማ የመቀራመቱ ዘመቻ ይቁም!
ትላንት ተዋሕዶን በማናናቅ ምእመናኑን ለማስኮብለል
ያልተሳካላቸው መናፍቃን፣ ዛሬ ደግሞ ስልት ቀይሰው
የተዋሕዶን ታሪክ፣ ግዕዝ ጠቀሳና ያሬዳዊ ዜማን ያደነቁ
በመምሰልየመፈታተናቸው አንድምታው ምን ይሆን?
የተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ለዘመናት ያቆየችውን ትውፊት፣
ቅርስና ሀብት የመቀራመቱ ድፍረትሳ ተመሳስሎ ተጠግቶ
ማንነትዋን ለመጋራት ይሆን?ዓላማው መጀመሪያ ምእመኑን
የማዘናጋት ቀጥሎ አንድነን ለማለትና ወደመናፍቅነት
ለመሳብ ከዚያም እንደ ሰለጠነው ዓለም ፍጹም ዓለማዊ
ለማድረግ ይሆንን?
መጽሐፍ ተዓቀቡኬ እምሐሳውያን ነቢያት እለይመጽኡ
ሀቤክሙ በአልባሰ አባግዕ፣ የበግ ለምድ ለብሰው ከሚመጡ
ሐሰተኞች፣ መናፍቃን፣ መምህራን ተጠንቀቁ፣ ወእንተ
ውስጦሙሰ ተኩላት መሰጥ እሙንቱ፡፡በውስጣቸው ግን ነጣቂ
ተኩላ ናቸው፣ ቢመረምሩዋቸው ግን ሰውን እየነጠቁ ወደ
ገኀነም የሚያወርዱ የሰይጣን ሰራዊት ናቸው፡፡ (ወንጌል
አንድምታማቴ 7፥15)
ይህን የወንጌል አሳብ እንደሚያስረዳን መናፍቃን ዓለማውያን
የሚጠነስሱት ሴራና ፈጠራ ጌታችን መድኀኒታችንኢየሱስ
ክርስቶስ ካስተማረው የማስጠንቀቂያ ትንቢት ቃል ውጭ
የሆነ ያልታወቀ፣ ያልተረዳአዲስ ነገር ሊሆን አይችልም፡፡
አስቀድሞ”በስሜ ይመጣሉ” ብሎ ተናግሯልና፡፡
ለዚህምቀጥሎ የተመለከተውን የበግ ለምድ ምሳሌ ዝርዘር
እንመልከት፣
1. የበግ ለምድ ለብሰው የሚመጡ ተኩላ ያላቸውእውነተኛ
መስለው የሚመጡ ሐሰተኞች መምህራንን ነው፣ ነገር ግን
በእውነተኛ ሃይማኖት ጸንተው ያሉትን ክርስቲያኖች
ተመሳስለው ገብተው በተለያየ ዘዴ ምእመኑን
በመቀሰጥናከእምነቱ በማናጋት ወደገሃነም ለማውረድ
የሚሠሩትን የዲያብሎስንሠራተኞች ነው፡፡
2. የበግ ለምድ መልበስምሳሌ
የሚያሳየውማስመሰያአሠራራቸውን፣ ድራማ መሰል
ጥረታቸውን ነው፡፡ተኩላ ለምድ የሚለብስሆኖ አይደለም፣
ተኩላ ለምድን ከሚለበስ ቢበላው ይመርጣልና፡፡ መናፍቃንም
የኢትዮጵያን ቤተ ክርስቲያን ባትኖር ይመርጣሉ፣ ነገር ግን
ሊውጡት ያሰቡትን ምእመን እንደ ተኩላ ለመንጠቅ
ያመቻቸው ዘንድ የቤተ ክርስቲያኗን ግእዝና ዜማ የወደዱ
መስለው መታየት የጀመሩትምእመኑን ለማዘናጋት የፈጠሩት
አዲሱ ዘዴ ነው፡፡ ነገር ግን ግብራቸው የተኩላ
ግብርእንዲመስል፣ ለነዚህ ቀሳጥያን ጌታችንአስቀድሞ
ሲመስልባቸው የበግ ለምድ ለብሰው የሚመጡ ተኩላ ነጣቂ
አላቸው፡፡ ይህም ተኩላ በግን ለመምሰል የበግን ቆዳ ቢለብስ
እንዳይዋሐደውና በግን እንዳይመስል እነሱም እንደ ድራማ
ትምህርቱን ልስበከው፣ ዜማውን ላዚመው፣ ቅዳሴውን
ልቀድሰው፣መዝሙሩን ልዘምረው ወዘተ ብለው ቢጥሩ
እውነተኛውን የተዋሕዶ አገልጋይ፣ አማኝእና ክርስቲያን
መሆን አይቻላቸውም፡፡
3. የበግ ለምድ የተባለው ምሳሌ፣ለምድ የበግ አካል የነበረ እንጂ
የተኩላ አካል አይደለም፣ተኩላው ከላይ ለምዱን ቢደርበው
አካል ሆኖት ደመ ነፍስ እንዳይዘራና ተኩላ በግ እንዳይሆን
ሁሉ መናፍቃንም የተዋሕዶን አሠራር ሳያምኑበት
በማስመሰልና ማቅረብ ቢሞክሩም እንኳን ውጤቱ ሕይወት
አልባ ዳንኪራ፣ በቀቢጸ ተስፋ ያቀረቡት ሙሾ
አስመስሎባቸዋል፡፡ በእሁኑ ወቅት የጀመሩት የተዋሕዶ
ምእመናን የሚወዱትን ግዕዝ መጥቀስ፣ ያሬዳዊ ዜማን
አስመስሎ ለማቅረብ የተሞከረው ሕይወት አልባ
እንቅስቃሴየዚህ ማሳያ ነው፡፡የተዋሕዶ ሕዝብ ማስተዋል
ያለበትይህን ሕይወት አልባ ሩጫ፣ ክርስቲያን ሳይሆኑ
ክርስቲያንን ለማታለል ያደረጉት የቅስጥ ድራማ መሆኑን
ነው፡፡
በወንጌል ትርጓሜ እነዚህን ቀሳጥያን በሁለት ዓይነት
ይገልጻቸዋል፣
1. ሃይማኖተኛ የሚመስሉ መናፍቃን መምህራን
2. መንፈሳውያን የሚመሰሉ ሥጋውያን መምህራን ይላቸዋል፡፡
እነዚህ የተጠቀሱት ሁለቱ በተገቢው ሃይማኖት ላልተረዱ
ሰዎች አደገኛ ናቸው፡፡ቅዱስ ጴጥሮስ እንዲህ በማለት
ይገልጻቸዋል ስለመናፍቅነታቸው፣ የዋጃቸውን ጌታ ክደው ...
የሚያጠፋ ኑፋቄ አሾልከው ያገባሉ፡፡ብዙዎችም
በመዳራታቸው ይከተሏቸዋል፡፡ ስለ ሥጋዊነታቸው ደግሞ ...
ይልቁንም በርኲሰት ምኞት የሥጋን ፍትወት እየተከተሉ
የሚመላለሱ ... ነውረኞችና ርኲሳን ... ምንዝር የሞላባቸው
ኀጢአትንም የማይተው ዓይኖች አሏቸው የማይጸኑትን ነፍሳት
ያታልላሉ፣ መመኘትን የለመደ ልብ አላቸው የተረገሙ ናቸው
(1ጴጥ 2፥1-16)ይላል፡፡
እነዚህ ሃይማኖተኛና መንፈሳውያን የሚመሰሉ የቤተ
ክርሰቲያን ጠላቶችን ከላይ ከቅዱስ መጽሐፍ እንደተገለጸው፣
ምእመናን ማንነታቸውንና ዓላማቸውን መረዳት አለብን፡፡
ማንነታቸው መጽሐፍ እንደጠቀሰው ተኩላነት ነው፣ ማለትም
ምንም ግእዝ ቢጠቅሱ ወይም ላላዋቂ ያሬዳዊ ዜማ
ያዜምኩ ቢመስሉ እነሱ በልባቸው ከሃዲያን ናቸው፡፡
ዓላማቸውም በመመሳሰልአቀራረብ ተቀባይነትን አግኝተው፣
ይህን እግዚአብሔርን የሚያከብር ሕዝብ ከእምነቱ ለማናጋት
ነው፡፡
በመመሳሰል ”የማይጸኑ ነፍሳትን ያታልላሉ” እንዲል፣
ክርሰቲያን ልብ ሊለው የሚገባው ዋናው ነገር፣ የተዋሕዶ
ተጻራሪዎች ሁሉ ሁል ጊዜ የመመሳሰል ስልታቸውን
በመቀያየር ያልጸኑትን ምእመንዋን መሻማት የዘመናት
አሠራራቸው እንደሆነ ነው፡፡ ለምሳሌ የፖርቱጋል ካቶሊክ
ሚሲዮናውያን የካቶሊክ እምነትን ወደ አገራችን ለማስገባት
በተለይ ቤርሙዴዝ፣ አንድሬ አብያዶ፣ ጴጥሮስ ፖኤዝና
አልፎኑስ ሜንደዝ ወዘተ ተልከው ነበር፡፡ ከእነዚህ አብዛኞቹ
ወደ አገራችን ሲመጡ ሆን ብለው አጥንተው ግእዝን
መናገርናየያሬዳዊን ዜማ እስከማዜም የደረሱ ነበሩ፡፡
እንዲያውም በሮም ቫቲካን የኢትዮጵያ ኮሌጅ በማቋቋም
የኢትዮጵያን ቤተ ክርስቲያንን ቋንቋግእዝን የሚናገሩና
ያሬዳዊን ዜማ የሚያዜሙ ነጮችን በመላክ የጎንደርን ቤተ
መንግሥት እንዴት ሲያተራምሱት እንደ ነበሩ
ታሪክያስረዳናል፡፡ ዛሬም የመመሳሰል ዓላማቸውን እውን
ለማድረግ በአገር ውስጥ እንቅስቃሴአቸው የተለያየ ገጽታዎች
ሲያሳዩ ይታያል፡፡ ለምሳሌ ይህንኑ ክብር ታቦትና ማኅሌት
የሚወድ ህዝብን ለማታለልና ወደራሳቸው ለማስገባት አንድ
ነን የሚል ስብከት፣ በዋና ዋና ከተሞች ባላቸው የጸሎት ቤት
ታቦት አለን፣ ማኅሌት ይቆማል ሲሉ፣ ፕሮቴስታንት በበዙበት
በሚመሰላቸው አካባቢ ደግሞ
ፕሮቴስታንትንመመሳሰልይስተዋልባቸዋል፡፡
ሌሎችምየመመሳሰል አባዜ የተጠናወታቸው መናፍቃን እና
ሥጋውያን እንደተለመደው ውጫውያንም ሆኑ የአገራችን
በተለይ ከተዋሕዶ የወጡ ማለትም በቀሳጢዎች የተበሉ
ካፈርኩ አይመልሰኝ እንዲል በቁጭት ሁል ጊዜ ይህንን
ሕዝብ በመጎምዠት ለአጋንንት አሳልፈው ለመሰጠት
ሲቋምጡና ለመንጠቅ ሲተጉይገኛሉ፡፡
ከላይ በግልጽ ለይተን አጽራረ ቤተ ክርስቲያንን ማንነት
ባጭሩ ማብራራት እንደሞከርነው ሁሉ፣ ለምን ስልታቸውን
መቀያየር አስፈለጋቸው የሚለውን ማየት ግድ ይለናል፡፡
ስልታቸውን መቀያየር ያስፈለገበት ምክንያት የተዋሕዶ
እምነትና ሥርዓት አንዳች የማመን ፍላጎት አድሮባቸው
አይደለም፡፡ ቤተ ክርስቲያኗን ሲወቅሱና ሲከሱ ነበርና፡፡
ለዚህ ምክንያት የደረሰባቸውን ክስረት መመልከት ተገቢ
ነው፡፡ ይህም፡-
1. የኢትዮጵያ ተዋሕዶ ቤተክርስቲያን ባደረገችው ጸረ ተሐድሶ
መናፍቃን ዘመቻ ህዝቡን በማስተማሯ ህዝቡ እኲይ
ተግባራቸውን ስለተረዳ
2. ህዝቡ ራሱ መልስ በመስጠት ራሱን መከላከል ስለጀመረ
3. በስህተት መንገዳቸው ተጉዞ የነበረው ሕዝብ ወደ ቤቱ
መመለስ ስለጀመረ
4. ቤተ ክርስቲያኗን በማጥላላት ያደረጉት ዘመቻ በመክሸፉ
እንደማያዋጣቸው ስለተረዱ
5. ከቤተ ክርሰቲያኗ ህዘቡን እየደለሉ በማስኮብለል የሚያገኙት
ይሁዳዊ ምንደኝነት ስለቀረባቸው
6. የካሴት ሽያጭ፣ የህዝቡ መዋጮ ወዘተ ገቢ ስለቀረባቸው ፤
ወዘተ ነው፡፡
ከላይ የተዘረዘረውና ሌላም የኪሳራ ምክንያቶቻቸውሳይወዱ
በግድ ልባቸውን ጸፍቶ አፋቸውን ከፍቶ አነጋግሯቸዋል፡፡
ክርስቲያኑ ሁሉ ይህን ሁኔታ በቀላሉ ማየትናበዝምታ ማለፉ
ተገቢ አይደለም፡፡ ይህ ሁሉ ክስረት ያናጋው መናፍቅ ከዚህ
የበለጠ ሌላ የድፍረት ዘዴ ለመፍጠር መሞከሩ አይቀሬ ነው፡፡
ሊሰመርበት የሚገባው ጉዳይበግእዝና በያሬዳዊ ዜማ
ያዘጋጁት ዝግጅት ገበያ ተኮርያውም የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ
ተዋሕዶ ምእመናንን ማእከል ያደረገ መሆኑን ነው፡፡
ልንረዳው የሚገባን አንዳንድ ምእመናን የማስመሰል
ተንኮላቸውን ባለመረዳት ካሴታቸውን መግዛትና ማዳመጥ
ሁለት አደጋ ያመጣባቸዋል፣ አንደኛው በመናፍቅ መንፈስ
የተዘጋጀው ዜማ ማዳመጥ ራሱ ቆይቶ መናፍቅ ሚያደርግ
መሆኑን፣ ሁለተኛው የመናፍቃን ከኪሳራቸው አንዱ ገንዘብ
በመሆኑ አማኙን ህዝብ የሚያስቱበትን ገንዘብ ለነሱ መገበር
ራሱ ከመናፍቅነት አይለይም፡፡
የአሁኑየለየላቸው መናፍቃን ወዳጅ የመምስል ስልታቸው
ከላይ ለመጥቀስ እንደተሞከረው ተኩላ በግን ለመምሰል ቆዳ
ብትደርት ተኩላነቷን እንዳይቀይር ሁሉ ምእመናንን ያታልላሉ
መስሎአቸው አንዴ ግእዙን አንዴ ዜማውን ያልኩ
ቢመስላቸውም ”ዪህቺ ጠጋጠጋ ... ” እንዲሉ ለእውነተኛ
ክርስቲያኖች ይህ መሰሪነታቸው ግልጽ ነው፡፡ በመሆኑም
ዓላማቸው የቤተክርስቲያን ተቆርቋሪ፣ ታሪኳን ተናጋሪ፣
ዜማዋን ወዳጅ፣ ጥንታዊነቷን አክባሪ ወዘተ በመምሰል
የህዝቡን ልብ ለማግኘት የተዘየደ ዘዴ ለማንም
አይጠፋውም፡፡ ነገር ግን ዘዴው ጊዜ ያለፈበት ድሮ በነ ዐጼ
ሱሱንዮስ ዘመን እነ አልፎኑስ ሜንደዝ የሞከሩት ነገር ግን
እነ ዐጼ ፋሲል አውቀውት ምላሽ የሰጡበት፣ የማይረሳ ጠባሳ
ጥሎ ያለፈ መሆኑ ወገኔ ትዝ ሊለው ግድ ይለዋል፣ የብዙ
ክርስቲያን ደም ተከፍሎበታልና፡፡ አሁንም ይህች መመሳሰልና
ቀይ መስመር መጣስ የነ አልፎኑስ ሜንደዝ ድፍረት ጋር አንድ
ናትና ከወዲሁ ካልታሰበባት በኋላ ከባድ ዋጋ እንዳታስከፍል
ስጋታችን ነው፡፡
ዋናው ጉዳይ ባለፈው በተካሄደው የጸረ ተሐድሶ ዘመቻ
መናፍቃን የፈራረሰባቸውን ሁለንተናዊ ክስረት ማለት በቤተ
ክርሰቲያኗ ውስጥ ምእመኑን መናፍቅ የማድረግ ቅሰጣ
ሲመታባቸውና ሴራው ሲከሽፍባቸው፣ ውድቀታቸውን መልሶ
ለመገንባት ስፖንሰራቸው የሰጣቸው አዲሱ አሰራር በግልጽ
ውዳሴ ለኢትዮጵያ ቤተ ክርስቲያንቋንቋ ግእዝ፣ ዜማዋ፣
ታሪኳ ወዘተ ማቅረብ ነው፡፡ ይህ የለየላቸው መናፍቃን ደርሶ
የቤተ ክርስቲያኗወዳጅ መምሰል ለኛ አዲስ ነገር አይደለም፤
ተሐድሶቹም ሲጠቀሙበት የነበረ ስልት ነው፡፡ የተሐድሶ
መናፍቃን ዘመቻ በኢትዮጵያ ቤተ ክርስቲያን ላይ በሚለው
መጽሐፍ (በኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን
በሰንበት ትምህርት ቤቶች ማደራጃ መምሪያየማኅበረ
ቅዱሳን ዶክሜንቴሽን ክፍል፣ ቁጥር 1፣ ሚያዝያ 2003
ዓም ገጽ 58) እንደተጠቀሰው ተሐድሶዎች ያቀዱት ዋና
ጉዳይ ተሐድሶ እንኳን እንደሆነ የማያውቅ ግን ተሐድሶ የሆነ
ትውልድ መፍጠር እና ሳያውቀው የሚደግፍ ቲፎዞ ማፍራት
ነበር፡፡ ማለትም በቤተ ክርስቲያኗ ውስጥ ሆኖ የመናፍቅን
ዶግማ የተቀበለ የእነሱን ዜማ የሚያዜም ወዘተ ቡድን
ማመቻቸት ነበረ፡፡ ስልቶቹን መጽሐፉ እንዲህ ይጠቅሳቸዋል፣
ተቆርቋሪ መምሰል፣ ገንዘብና እርዳታ በመስጠት፣ የቤተ
ክርስቲያኒቱን ተቋማትና ሕዝቡን መያዝ እና ቲፎዞ እንዲሆን
ማድረግ፣
ኦርቶዶክስን የማያውቅ፣ ፕሮቴስታንት የሆነ፣ ነገር ግን
ተሐድሶ (ፕሮቴስታንት) መሆኑን እንኳ የማያውቅ ምእመን
ማፍራት፡፡ ማተብ ያሰረ፣ ነጠላ የሚያጣፋ፣ እምነቱና መንፈሱ
ግንፕሮቴሰታንት የሆነ፣ ሆኖም ፕሮቴስታንት ነኝ የማይል
(ፕሮቴስታንት መሆኑን ሳያውቅ ስለተለወጠ)፣ ”እኔ
ኦርቶዶክስ ነኝ” እያለ የሚናገር(ሀርድ ዌሩ ሳይቀየር ሶፍት
ዌሩ የተቀየረ)ትውልድ ማፍራት ነው፡፡
እንዲሁም በዚህ ወቅት ፕሮቴስታንቱ በግልጽ መሰደቡንና
መወገዙን በውስጥ አድርገው በውጪ ውዳሴ የጀመሩት፣
የኦርቶዶክስ ምእመናንን በመመሳሰል ለመሳብና ቢቻላቸው
ፕሮቴስታንት ለማድረግ ባይሆንም ቲፎዞ ለማድረግ፣
እንዲሁም ቲፎዞ በመሆን መካከል በሚፈጠረው
ያለመግባባት ክፍተት ያልጸኑትን ለማግኘት ነው፡፡
ባጠቃላይምከላይ እንደገለጽነው መናፍቃን ምን ጊዜም
የተወሰነ ሃይማኖታዊ የትውፊት፣ የዶግማ፣ የሥርዓት ወዘተ
ገደብ የሌላቸው በመሆኑ የሌላውን መንጋ ለመቀሰጥ
ቢቻላቸው በማጥላላት ባይቻላቸው በመመሳሰል ራሳቸውን
እየለዋወጡ የተለያየ ስልት እንሚጠቀሙ መረዳት ተገቢ
ነው፡፡ ለመመሳሰል በሚያደርጉት ቅሰጣ የኦርቶዶክስ ተዋሕዶ
ቤተ ክርስቲያን ለዘመናት ያቆየችውን ትውፊት፣ ቅርስና ሀብት
እንዲሁም ግእዝ ቋንቋና ያሬዳዊ ዜማን ማንም እንደፈለገ
አስመስሎ ባልተገባ መንገድ የመቀራመቱ ድፍረት ቤተ
ክርስቲያን እንዴት ታየዋለች? ያውም ቤተ ክርስቲያን
የማትፈቅደው የመናፍቅ ድርጅት በሀብቷ ላይ ሲፈነጭ፣ ይህስ
ጉዳይ ከህግ አንጻር እንዴት ይታያል? አንድ ተቋም ያላትን
ሀብት ያለፈቃዷ ማንም መጠቀም ይችላልን? ምእመናን
በሙሉ በተለይ የሕግ ባለሙያ ልጆቿ እንዲነጋገሩበት
የሚስፈልግ ጉዳይ ነው፡፡ ሌላው ምእመናን መገንዘብ
የሚገባን መናፍቅ ያወጣውን የቅስጥ ዜማ ያሬዳዊ መስሎን
በመጠቀም የዓላማቸው ሰለባ እንዳንሆን አንዱ ለሌላው
ማሳሰብና ማስረዳት ተገቢ ነው፡፡ ጌታችን መድኀኒታችን
ኢየሱስ ክርስቶስ የበግ ለምድ ለብሰው ማለት እውነተኞች
መስለው ከሚመጡ ሐሰተኞች፣ ሃይማኖታውያን መስለው
ከሚመጡ መናፍቃን፣ መንፈሳውያን መስለው ከሚመጡ
ሥጋውያን መምህራን ተጠንቀቁ ብሎ አስተምሮናልና
እንጠንቀቅ፣ እርስ በርሳችንም እንጠባበቅ፡፡
ወስብሐት ለእግዚአብሔር ወለወላዲቱ ድንግል ወለመስቀሉ
ክቡር አሜን፡፡

happy new year!!!

እንኳን ከዘመነ ዮሐንስ ወደ ዘመነ ማቴዎስ በሰላም አሸጋገረን by eyasu etsub
እንኳን ከዘመነ ዮሐንስ ወደ ዘመነ ማቴዎስ በሰላም አሸጋገረን እያልን መጪው ዘመን ካሳለፍናቸው ቅዱሳን አባቶች ታሪክ ብዙ የምንማርበት ያለብንን ደካማ ጎን
የምንፈትሽበት ሊሆን ያስፈልጋል፡፡ ያለፉት አባቶቻችን ብዙ ሥራ ሠርተው የብርሃን ችቦ አብርተው በክብር አስረክበውን አለፉ፡፡
ገና እነ ቅዱስ ጳውሎስ ክርስትናን ሳይቀላቀሉ አባታችን ባኮስ ክርስትናን ከሐዋርያት ተቀብሎ ወደ ሀገሩ ተመልሶ በማስተማር በዓለም የመጀመሪያው ተብሎ በታሪክ ላይ
ተመዝግቦ ኢትዮጵያዊ ጃንደረባ ብርሃነ ወንጌልን በመቅረዝ ላይ ለኮሰ፡፡ በዚህም ትምህርቱ ቤተክርስቲያን በራሷ ሐዋርያ
ወንጌልን ተሰብካ በኢየሩሳሌም ላይ ጥምቀትን ፈጽማ የመጀመሪያው አድርጓት ለሌሎች ወንድሞች አስረከበ፡፡ እነ
ከሳቴ ብርሃን አባ ሰላማ፣ ዘጠኙ ቅዱሳን፣ ቅዱስ ያሬድ ሌሎችንም ጨምሮ ታላቅ ሥራን ሠርተው ለቀጣዩ ትውልድ
አስረከቡ፡፡ ክርስትና ሃይማኖትን ከምግባር ዶግማን ከቀኖና ታሪክን ከትውፊት ሥራን ከቅርጽ አስረክበውን የብርሃኑን ችቦ
ለኩሰው ብርሃንን ገልጠው አለፉ፡፡
የአክሱም አሻራዎች፣ የመርጦ ለማርያም፣ የተድባበ ማርያም፣ የጣና ቂርቆስና ሌሎቹም እጅግ ብዙ ቅርጾች አሁን ሕያው ሆነው የሚታዩንን ሁሉ አስረክበው ወደ ገነት
ታደሙ፡፡ አዲስ የሥነ ጽሑፍ ዘርፍ ብቻ ሳይሆን በያሬዳዊ ዜማ እግዚአብሔርን በዝማሜ በመርግድ በጽሕፋትና
በወረብ ማመስገንን /አቋቋምን/ አሁንም በእግዚአብሔር ጥበብ ተቀብለው ወደ ሚቀጥለው ዓለም ተሻገሩ፡፡ እነዚህ
ሁሉ አባቶቻችን ክርስትናን ተቀብለው ሲያስረክቡን በቀላሉና በተደላደለ ሁኔታ አልነበረም እሳት ዳር ሆነው ሳይሆን እሳት
ላይ ሆነው መከራን ተቀብለው ነው፡፡ እኛስ ዛሬ የዘመኑ አባቶች ካህናት ሰንበት ት/ቤቶች እና ምዕመናን ለመጪው ተውልድ ምን ለማስረከብ ተዘጋጅተናል? ዛሬ ከእኛ
ቤተክርስቲያን ብዙ ነገር ትጠብቃለች፡፡ ከኛም ዛሬ ከሚጠበቀው ነገር አንዱና ትልቁ ነገር በቤተክርስቲያን ዙሪያ ያለውን የፈተና እሳት ለማጥፋት ዳር ላይ ቆመን ሳይሆን እሳት
ውስጥ ቆመን እሳቱን ለማጥፋት ከእኛ ብዙ ይጠበቃል፡፡
ብንችል አዲስ ታሪክ ለመስራት ባንችል ደግሞ ያለውን ታሪክ ለማስጠበቅ ሁላችንም ባለን ጸጋ ቤተክርስቲያናችንን ለመጥቀም እና ልናገለግላት ቃል የምንገባበት ዘመን ሊሆን
ይገባል፡፡ ለዚህ ደግሞ የሰንበት ት/ቤት ወጣቶች ካህናት እና የሰበካ ጉባኤያት በማኅበረሰቡ ውስጥ ያሉ መሆናቸው
ያሰብነውን ራዕይ ለማሳካት ይረዳናል፡፡ ስለሆነም መጪው ዘመን ዘመነ ማቴዎስ ለቤተክርስቲያን እንደቀደሙት አባቶች
መልካም አባት የምታገኝበት እኛም ልጆች ለቤተክርስቲያን የምንቆምላት ዘመን እንዲሆን ልንጸልይ ይገባል፡፡

The ten commandments


ክርስቲያናዊ ሥነ - ምግባር
አሥርቱ ትዕዛዛት
ከእግዚአብሔር አምላክ በቀጥታ በሙሴ አማካኝነት ለእስራኤላውያን የተሰጠ ሕግ ነው፡፡ የተሰጡትም እስራኤላውያን ከግብጽ ከወጡ በ3ኛው ወር ፋሲካን ካከበሩ
በ3ኛው ቀን በደብረ ሲና ሰፍረው ሳለ ነበር፡፡ ዘፀ. 19፡1-4
በዘዳ. 34፡28 ዘዳ. 4፡13 ላይ አሥሩ ትዕዛዛት አሥር መሆናቸውን እንረዳለን፡፡
በዝርዝር ተጽፈው የሚገኙት ግን በዘዳ. 20፡ 3 እና17 ዘዳ. 5፡5-21 ላይ ነው፡፡ አሥርቱ ቃላትና ስድስቱ ቃላተ ወንጌል ለእስራኤል ዘስጋና ለእስራኤል ዘነፍስ የተዘጋጁ
ስለሆነ ሁላችንንም ይመለከታል፡፡ እነርሱም፡-
1. ‹‹ እግዚአብሔር አምላክህ እኔ ነኝ፡፡ ከእኔ በቀር ሌሎች አማልክት አይሁኑልህ የማናቸውንም ምሳሌ የተቀረጸውን
ምስል ለአንተ አታድርግ፤ አትስገድላቸው፤ አታምልካቸው ››ዘፀ. 20፡2-6
2. ‹‹ የእግዚአብሔር የአምላክን ስም በከንቱ አትጥራ፡፡ ››ዘፀ. 20፡7
3. ‹‹ የሰንበትን ቀን ትቀድሰው ዘንድ አስብ /አክብረውም/›› ዘፀ. 20፡ 8
4. ‹‹አባትህንና እናትህን አክብር››ዘዳ.20፡12
5. ‹‹ አትግደል ›› ዘፀ. 20፡13
6. ‹‹ አታመንዝር ›› ዘፀ. 20፡14
7. ‹‹ አትስረቅ ›› ዘፀ. 20፡15
8. ‹‹ በሐሰት አትመስክር ›› ዘፀ. 20፡16
9. ‹‹ አትመኝ ›› ዘፀ. 20፡17
10. ‹‹ ባልንጀራህን እንደ ራስህ ውደድ ›› ዘሌ. 19፡18
- አሥርቱ ሕግጋት የብሉይ ኪዳን መሠረቶች ናቸው፡፡የእግዚአብሔርን ሕግ ብትጠብቁ ብትፈጽሙትም ሕዝቤ
ትሆናላችሁ እኔም አምላክ እሆናችኋለሁ ብሎ ቃልኪዳን ገባ፡፡
ሕዝቡም በአንድ አፍ ድምጻቸውን ከፍ አድርገው
‹‹እግዚአብሔር ያለውን ሁሉ እናደርጋለን እንታዘዛለን››ብለው ቃል ኪዳን ገቡ፡፡ ዘፀ. 19፡8፤ 24፡1-8 ቅዱስ ጳውሎስም እንደነገረን ይህ ፊተኛው ኪዳን ያለ ደም
አልተመረቀምና ዕብ. 18፡ 22 ሙሴ ኪዳኑን ለማጽናት የደም መርጨትን ሥርዓት እንዳደረገ በሐዲስ ኪዳንም ቢሆን
ሥነ ሥርዐቱ ሙሉ በሙሉ ተቀባይነት ያላቸው ሕግጋት ናቸው፡፡ ማቴ 5፡17፣ 19፡15-22 ፣ዮሐ1፡12
እግዚአብሔር ሕዝቦቹና ልጆቹ ሊያረገን ይህን ታላቅ ተስፋ በመስጠት ቃል ከገባልን እኛ ደግሞ ትዕዛዙን ለመጠበቅ ምን
ያህል ቃል ገብተንለታል? ጌታችን ብትወዱኝስ ትዕዛዜን ጠብቁ ዮሐ 14፡15 እንዲሁም ከሆነ እንደ እስራኤላውያን
እግዚአብሔር ያለውን ሁሉ እናደርጋለን እንታዘዛለን ብለንከሁሉ በፊት ለእግዚአብሔር ቃል መግባት አለብን፡፡ክርስትናውን ስንጀምር የመጀመርያ ሥራችን መሆን ያለበትይህ ነው፡፡
የዐሥርቱ ትዕዛዛት ዓላማ
ዐሥርቱ ትዕዛዛት የተሰጡት በሚከተሉት ዓላማዎች ነው፡፡ይኸውም፡-
1. ከግብጽ ምድር ስላወጣቸው ውለታውን እንዲያስቡ
2. ወደ ፊት በአረማዊያን መካከል ሲመላለሱ ከኃጢአት እንዲቆጠቡ
3. መንፈሳዊ አካሄዳቸው ምን ምን አቅጣጫ መከተል እንዳለበት ለማሳየት ነው፡፡